tg-me.com/orthodoxzelalemawit/6629
Last Update:
“እኔ የነገርኋችሁ ቃል መንፈስ ነው ሕይወትም ነው።” (ዮሐ. 6፥63)
***
የክርስትና አስተምህሮ አመክንዮአዊ ቀመር እና የቃላት ብያኔ ብቻ አይደለም። ጌታችን እንደነገረን ከዚያ የሚያልፍ መንፈስ ነው፤ ሕይወትም ነው። በመሆኑም አንድ ንባብ በቅዱሳት መጻሕፍት ቢገኝም 'መንፈሱን' ካልተረዳን እንስታለን። ያ አገላለጽ የተነገረው ምንን ለማጠየቅ ነው? ምን ብለን ብንረዳው ደግሞ ስህተት ይሆናል? ብሎ ትውፊታዊ መረዳትን ይጠይቃል። አንዳንዶቹ አገላለጾች ደግሞ እጅግ ትልቅ ቅጥነተ ህሊና ይጠይቃሉ። ከእነዚህ አንዱ 'ፈጣሪ ወፍጡር' የሚለው ትምህርት ነው።
ሁለት ባህርይ የሚሉ ካቶሊኮች እንኳ ክርስቶስን 'በሥጋው ፍጡር' ማለት በትክክለኛ ዓውዱ ከተነገረ ስህተት ባይሆንም ምእመናን እንዳይደናገሩ በነገረ ሃይማኖት ሐተታዎች ውስጥ በብዛት አንጠቀመውም ይላሉ። (Catholic Encyclopedia)
ይህ ጥንቃቄ በቤተ ክርስቲያናችን ትውፊት ውስጥም ያለ ነው። እኔ እስከማውቀው በአምልኮ መጽሐፎቻችን ውስጥ አይነገርም። እጅግ አልፎ አልፎ የሚገኘው በአንዳንድ ሊቃውንት ድርሳናት ውስጥ ነው። ይህ የሚያመለክተው አገላለጹ በቅጥነተ ህሊና ከነሙሉ ዓውዱ ካልተረዱት ምእመናን 'በሥጋው ፍጡር ስለሆነ በሥጋው አናመልከውም' ብለው እንዳይሰናከሉ ነው።
'ክርስቶስ በሥጋው ፍጡር ነው' ሲባል፦
1. የለበሰው ሥጋ ዘላለማዊ ህልውና ያልነበረው የእኛ የተፈጠረ እውነተኛ ሥጋ ነው ለማለት ነው።
2. የሰው ልጆች ሐዲስ ተፈጥሮ (መታደስ) ከእርሱ የተጀመረበት ዳግማይ አዳም፣ በኲረ ፍጥረታት መሆኑን ለመናገር ነው። ቅዱስ ጎርጎሬዎስ ዘእንዚናዙ እንዳለው ያልነሳውን አላዳነምና።
3. ሌሎችም።
***
ነገር ግን ከነዚህ እሳቤዎች መጠንቀቅ ደግሞ ይገባል፦
1. 'ክርስቶስ በሥጋው ፍጡር ነው' ማለት በሥጋው አምልኮ አይገባውም ማለት አይደለም። የክርስቶስን ሥጋ ከመለኮቱ ለይተን በመለኮቱ ብቻ እናምልክ ካልን የማይከፈለውን አንዱን ክርስቶስን እየከፈልነው ነው፤ ስለ መዳናችን ሰው የሆነውን ክርስቶስን ስለእኛ ሰው በመሆኑ ዝቅ እያደረግነው ነው። ስለ ሕዝቡ ሲል ከአባቱ ዙፋን ወርዶ ሕዝቡ የሚለብሱትን መናኛ ልብስ ለብሶ የሚታደገውን የንጉሥ ልጅ ውለታ ባለመረዳት 'በዚህ ሁኔታ እንደ ንጉሥ አናይህም' ብሎ እንደመሳለቅ ነው።
2. 'ክርስቶስ በሥጋው ፍጡር ነው' ማለት በሥጋው ማኅየዊ (ሕይወትን የሚሰጥ) አይደለም ማለት አይደለም። ይህ ቢሆን ቅዱስ ቄርሎስ እንዳለው ሥጋውን እና ደሙን መቀበል ከንቱ በሆነ!
3. 'ክርስቶስ በሥጋው ፍጡር ነው' ማለት በሥጋው ለአብ ይገዛል ማለት አይደለም። አብ ከፍ ከፍ አደረገው፣ ከስሞች ሁሉ በላይ የሆነ ስምን ሰጠው የተባለ በሥጋው ነው። ታዲያ ይህ ከፍታ ከመገዛት የማያወጣ ከሆነ ከቅዱሳን የጸጋ ክብር በምን በለጠ? ቅዱስ አትናቴዎስ እንዳለው ከፍጡራን ግብርናት እስካልወጣ ድረስ ምን ቢከብር ለእርሱ የሚገባ ክብር አይደለም። በቅዱሳት መጻሕፍት ስለ ክርስቶስ የተነገሩ የትሕትና ንግግሮች ከማዳን ግብሩ እና አርአያነቱ (economy of salvation) አንጻር የምንረዳቸው ናቸው። ካልሆነ ግን በክርስቶስ ዘንድ ሰው ከመሆኑ የተነሣ ዘላለማዊ ተዋርዶ ገብቷል ያስብላል።
በሥላሴ አካላት ዘንድ ከአንዱ ወደሌላው የሚፈስ ዘላለማዊ ክብርና ምሥጋና አለ። ነገር ግን ሰው ከመሆኑ የተነሣ በወልድ ዘንድ የፍጡር አምልኮ ግዴታ አልወደቀበትም። ቅዱስ ጎርጎሬዎስ ዘእንዚናዙ እንዳለው ይህን አብም አይፈልግም፤ ወልድም አይሰጥም።
Bereket Azmeraw
BY አንዲት እምነት ✟✟✟
Warning: Undefined variable $i in /var/www/tg-me/post.php on line 283
Share with your friend now:
tg-me.com/orthodoxzelalemawit/6629